አምስቱ የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ይግባኝ ተጠየቀባቸው

ባለፈው ሚያዝያ 2006 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ታስረው ፣ጉዳያቸው ለአንድ ዓመት ከ5 ወር በላይ ሲታይ ቆይቶ ከበፈቃዱ ኃይሉ በስተቀር ቀሪዎቹ “መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ” ተብሎ ከሁለት ወራት በፊት የተወሰነላቸው አምስቱ የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ይግባኝ ተጠየቀባቸው፡፡

የፌደራል ዐቃቤ ሕግ በአምስት የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ላይ ባቀረበው ይግባኝ መሠረት ለቃል ክርክር ተዘጋጅተው እንዲቀርቡ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የወንጀል ችሎት ማዘዙ ተሰምቷል፡፡

 

ፍርድ ቤቱ በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለሚከራከሩት አምስት የዞን ዘጠኝ አባላት መጥሪያውን ያወጣው ታህሣሥ 4 ቀን 2008 ዓ.ም ሲሆን፤ ለቃል ክርክር ቀነ-ቀጠሮ የሰጠው ለፊታችን ታህሣሥ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 2፡30 መሆኑን መጥሪያው ያስረዳል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ መጥሪያው የደረሰው ለበፍቃዱ ኃይሉ ብቻ ሲሆን፤ በተሰጠው የቃል ክርክር ቀነ-ቀጠሮ እንዲቀርቡ መጥሪያ የወጣላቸው በፈቃዱ ኃይሉ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ከዚህ ቀደም፤ በፍቃዱ ኃይሉ የተቀየረለትን “አመፅ የማነሳሳት” የወንጀል አንቀፅ ለመከላከል ለጥር 30 ቀን 2008 ዓ.ም. መቀጠሩ አይዘነጋም።

Source: http://addismedia.info/

Leave a comment